አሁን እግዚአብሔር በሕይወቴ ይኖራል?

ኢየሱስን ወደ ሕይወትህ እንዲገባ የመጋበዝ ውሳኔ ስታደርግ፣ እግዚአብሔር እንደሰማህ ማወቅ ያስፈልግሃል፡፡ አዎን ሰምቶሃል? እኛ ግባ ብለን ከጋበዝነው፣ ወደ ሕይወታችን እንደሚገባ ኢየሱስ ተስፋን ሰጥቶናል፡፡

በራእይ 3፡20 ውስጥ ኢየሱስ ይህንን ጥሪ አቅርቧል፣ “እነሆ በደጅ ቆሜ አንኳኳለሁ፤ ማንም ድምጼን ቢሰማ ደጁንም ቢከፍትልኝ፣ ወደ እርሱ እገባለሁ ከእርሱም ጋር እራት እበላለሁ እርሱም ከእኔ ጋር ይበላል፡፡” የልብህን በር ለእግዚአብሔር ከፍተሃል? ከከፈትህ፣ እርሱ ምን አደርጋለሁ አለ? እግዚአብሔር ወደተሳሳተ መንገድ ይመራሃልን?

1ኛ ዮሐንስ 5፡14 እንዲህ ይላል፣ “በእርሱ ዘንድ ያለን ድፍረት ይህ ነው፤ እንደ ፈቃዱ አንዳች ብንለምን ይሰማናል”፡፡

በዮሐንስ 6፡37 ውስጥ፣ ኢየሱስ እንዲህ ይላል፣ “አብ የሚሰጠኝ ሁሉ ወደ እኔ ይመጣል፣ ወደ እኔም የሚመጣውን ከቶ ወደ ውጭ አላወጣውም፤” በዮሐንስ 10፡27-29 ኢየሱስ እንዲህ ብሏል፣ “በጎቼ ድምፄን ይሰማሉ እኔም አውቃቸዋለሁ ይከተሉኝማል፤ እኔም የዘላለም ሕይወትን እሰጣቸዋለሁ፣ ለዘላለምም አይጠፉም፣ ከእጄም ማንም አይነጥቃቸውም፡፡ የሰጠኝ አባቴ ከሁሉ ይበልጣል፣ ከአባቴም እጅ ሊነጥቃቸው ማንም አይችልም፡፡”

ከእርሱ ጋር ኅብረት ይኖረን ዘንድ፣ ኢየሱስ ስለ ኃጢአታችን ሲል በመስቀል ላይ ሞተ፡፡ ጉዳዩን አስመልክቶ የተምታታ አቋም የለውም፡፡ እኛን ከእርሱ ጋር ኅብረት እንዲኖረን ለማድረግ ረጅም ርቀት ተጉዟል፡፡ ኢየሱስ የእኛን ኃጢአት በራሱ ላይ አደረገ እኛን ደግሞ በእርሱ ጽድቅ ሸፈነን፣ በእርሱም ዘንድ ሙሉ በሙሉ ይቅርታንና ተቀባይነትን ያገኘን አደረገን፡፡ አስቀድመን በጎ ተግባራትን ማከናወን፣ ሃየይማታዊ ወጎችን መጠበቅ ወይም እርሱን በመለመን ዓመታትን ማሳለፍ አላስፈለገንም፡፡ ከእርሱ ጋር ኅብረት እንዲኖረን ማድረግ የሚችል እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ ወደ እርሱ የመጣነው እርሱ ለእኛ ባደረገው መሠረት እንጂ፣ እኛ ለእርሱ ባደረግነው መሠረት አየይደለም፡፡ ይቅር ይለንና ወደ ሕይወታችንም ይመጣ ዘንድ የኃጢአት እዳችንን ከፈለ፡፡ 1ኛ ጴጥሮስ 3፡18 እንዲህ ይላል፣ “ክርስቶስ ደግሞ ወደ እግዚአብሔር እንዲያቀርበን እርሱ ጻድቅ ሆኖ ስለ ዓመፀኞች አንድ ጊዜ በኃጢአት ምክንያት ሞቶአልና፤”

አንድ ሰው ኢየሱስን ወደ ሕይወቱ እንዲገባ ሲጠይቅ፣ ከእግዚአብሔር ጋር የሚኖረውን ግንኙነት አስመልክቶ እግዚአብሔር የተናገረው ነገር እውነተኛ መሆኑን ማወቅ አስደናቂ ነው፡

  • ከእግዚአብሔር ጋር ሰላም አለህ -

    “እንግዲህ በእምነት ከጸደቅን በእግዚአብሔር ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሰላምን እንያዝ፤” (ሮሜ 5፡1)

  • የእግዚአብሔር ልጅ ሆነሃል -

    “ለተቀበሉት ሁሉ ግን፣ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፡፡ ” (ዮሐንስ 1፡12)

  • ከእንግዲህ በጨለማ አትመላለስም -

    “ቀድሞ ጨለማ ነበራችሁና፣ አሁን ግን በጌታ ብርሃን ናችሁ፤ … እንደ ብርሃን ልጆች ተመላለሱ” (ኤፌሶን 5፡8፣9)

    “እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፣ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን፡፡” (ቆላስይስ 1፡13፣14)

  • ይቅር ተብለሃል -

    “በእርሱ የሚያምን ሁሉ በስሙ የኃጢአቱን ስርየት እንዲቀበል ነቢያት ሁሉ ይመሰክሩለታል፡፡” (የሐሥ 10፡43)

    “በውድ ልጁም፣ እንደ ጸጋው ባለጠግነት መጠን፣ በደሙ የተደረገ ቤዛነታችንን አገኘን እርሱም የበደላችን ስርየት፡፡ ጸጋውንም በጥበብና በአዕምሮ ሁሉ አበዛልን፡፡” (ኤፌሶን 1፡7-8)

    “በዚህ የእግዚአብሔር ፍቅር በእኛ ዘንድ ተገለጠ፣ በእርሱ በኩል በሕይወት እንኖር ዘንድ እግዚአብሔር አንድ ልጁን ወደ ዓለም ልኮታልና፡፡ ፍቅርም እንደዚህ ነው፤ እግዚአብሔር እርሱ ራሱ እንደ ወደደን ስለ ኃጢአታችንም ማስተሰረያ ይሆን ዘንድ ልጁን እንደ ላከ እንጂ እኛ እግዚአብሔርን እንደ ወደድነው አይደለም፡፡”(1ኛ ዮሐንስ 4፡9-10)

  • የዘላለም ሕይወት ተሰጥቶሃል -

    “እውነት እውነት እላችኋለሁ፣ ቃሌን የሚሰማ የላከኝንም የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፣ ከሞትም ወደ ሕይወት ተሻገረ እንጂ ወደ ፍርድ አይመጣም፡፡” (ዮሐንስ 5፡24)

    “እግዚአብሔርም የዘላለምን ሕይወት እንደሰጠን ይህም ሕይወት በልጁ እንዳለ ምስክሩ ይህ ነው፡፡ ልጁ ያለው ሕይወት አለው፤ የእግዚአብሔር ልጅ የሌለው ሕይወት የለውም፡፡ የዘላለም ሕይወት እንዳላችሁ ታውቁ ዘንድ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ለምታምኑ ይህን ጽፌላችኋለሁ፡፡” (1ኛ ዮሐንስ 5፡11-13)

  • በመንፈስ ቅዱስ ታትመሃል -

    “እናንተም ደግሞ የእውነትን ቃል፣ይኸውም የመዳናችሁን ወንጌል ሰምታችሁ ደግሞም በክርስቶስ አምናችሁ፣ በተስፋው መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ ታተማችሁ፤ እርሱ የርስታችን መያዣ ነው፣ ለእግዘዚአብሔር ያለውን ሁሉ እስኪዋጅ ድረስ፣ ይህም ለክብሩ ምስጋና ይይናል፡፡” (ኤፌሶን 1፡13-14)

  • እግዚአብሔር ለአንተ ያለውን ፍቅር ማወቅ ትጀምራለህ -

    “በእኔ ብትኖሩ ቃሎቼም በእናንተ ቢኖሩ የምትወዱትን ሁሉ ለምኑ ይሆንላችሁማል፡፡ ብዙ ፍሬ ብታሩና ደቀመዛሙርቴ ብትሆኑ በዚህ አባቴ ይከበራል፡፡ አብ እንደ ወደደኝ እኔ ደግሞ ወደድኋችሁ፤ በፍቅሬ ኑሩ፡፡ እኔ የአባቴን ትእዛዝ እንደ ጠበቅሁ በፍቅሩም እንደምኖር፣ ትእዛዜን ብትጠብቁ በፍቅሬ ትኖራላችሁ፡፡ ደስታዬም በእናንተ እንዲሆን ደስታችሁም እንዲፈጸም ይህን ነግሬአችኋለሁ፡፡” (ዮሐንስ 15፡7-11)

ከእግዚአብሔር ጋር ባለህ ግንኙነት ለማደግ፡

እርሱን ይበልጥ ለማወቅ፣ ቃሉን (መጽሐፍ ቅዱስን) ለማንበብ ጊዜ ለመውሰድ፣ ራሱን ለአንተ ይበልጥ እንዲገልጥልህና አንተ ከእርሱ ጋር ግንኙነት እንድትመሠርት እንዲረዳህ ለመጠየቅ፣ የዮሐንስ ወንጌል (በአዲስ ኪዳን አራተኛው መጽሐፍ) ለመነሻነት ጥሩ መጽሐፍ ነው፡፡

ከእርሱ ጋር በነፃነት ተነጋገር፡፡ “በነገር ሁሉ በጸሎትና በምልጃ ከምስጋና ጋር በእግዚአብሔር ዘንድ ልመናችሁን አስታውቁ እንጂ በአንዳች አትጨነቁ፡፡ አእምሮንም ሁሉ የሚያልፍ የእግዚአብሔር ሰላም ልባችሁንና አሳባችሁን በክርስቶስ ኢየሱስ ይጠብቃል፡፡” (ፊልጵስዩስ 4፡6፣7)